MEXC የኢትዮጵያ ብርን ከP2P (Peer-to-Peer) የግብይት ሥርዓቱ ላይ አስወገደ
ዜና ቴክ⭐ Featured Story

MEXC የኢትዮጵያ ብርን ከP2P (Peer-to-Peer) የግብይት ሥርዓቱ ላይ አስወገደ

Written byADMIN
PublishedJune 10, 2026
Read Time5 min Read

ዓለም አቀፉ የክሪፕቶ መድረክ MEXC የኢትዮጵያ ብር የP2P ግብይትን ከቀጠሮው ቀድሞ በድንገት አቋርጧል። ይህም ሌሎች የክሪፕቶ ግብይት ተቋማት ያደረጉትን ማፈግፈግ ያጠናቀቀ ሆናል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በበኩሉ ጥብቅ ቁጥጥር እያደረገ ቢሆንም ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ፋይናንስ ሥርዓት ለመፍጠር የሕግ ማዕቀፍ እያጠና ይገኛል።

ዓለም አቀፉ የክሪፕቶ ምንዛሬ መድረክ MEXC የኢትዮጵያ ብርን (ETB) ከP2P (Peer-to-Peer) የግብይት ሥርዓቱ ላይ ሙሉ በሙሉ እና በድንገትአቃረጠ።

ኩባንያው ቀደም ሲል ይህንን አገልግሎት የሚያቆመው እ.ኤ.አ. ሰኔ 30 ቀን 2026 መሆኑን ገልጾ የነበረ ቢሆንም ይፋ ባላደረገው ምክንያት ከተቀመጠው ቀነ-ገደብ ሃያ ቀናት ቀድሞ ውሳኔውን ተግብሯል።

በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጵያ ብር (ETB) ምርጫ ከፕላትፎርሙ ላይ ሙሉ በሙሉ በማጥፋቱ አስቀድመው ዝግጅት እያደረጉ ለነበሩ የአገር ውስጥ የክሪፕቶ ተጠቃሚዎች እና ነጋዴዎች ያልተጠበቀ ድንጋጤን ፈጥሯል።

ይህ የMEXC ድንገተኛ እርምጃ በኢትዮጵያ የክሪፕቶ ገበያ ላይ የተከሰተ አዲስ ክስተት አይደለም። ከዚህ ቀደምም የአገሪቱን የፋይናንስ ሕግ እና ጥብቅ መመሪያዎችን መሠረት በማድረግ ባይናንስ (Binance)፣ ባይቢት (Bybit)፣ ቢትጌት (Bitget)፣ ኦኬኤክስ (OKX) እና ቴሌግራም ዋሌት (Telegram Wallet) የመሳሰሉ ታዋቂ ዓለም አቀፍ የክሪፕቶ መድረኮች በኢትዮጵያ ብር የሚደረጉ የP2P ግብይቶችን በተከታታይ ማቆማቸው ይታወሳል።

የMEXC ውሳኔም የክሪፕቶ የግብይት መድረኮች አሰራር ከአገሪቱ የቁጥጥር ሥርዓት ጋር ለማጣጣም የሚያደርጉትን ማፈግፈግ ሙሉ በሙሉ ያጠናቀቀ ክስተት ሆኗል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በበኩሉ ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን ለመግታትና የፋይናንስ ሥርዓቱን መረጋጋት ለመጠበቅ ጥብቅ ቁጥጥር እያደረገ ይገኛል። ይሁን እንጂ፣ ባንኩ ከእገዳዎች ባሻገር ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ግልጽነት እና የቁጥጥር ሥርዓት ያለው የዲጂታል ፋይናንስ ተሳትፎ በአገሪቱ መፍጠር የሚቻልበትን ሁኔታ እያጠና መሆኑን ገልጿል።

ለዚህም ይረዳው ዘንድ አጠቃላይ የቁጥጥርና የሕግ ማዕቀፍ ለማዘጋጀት ከዓለም አቀፍ አቻ ተቆጣጣሪ ተቋማት እና ከአገር ውስጥ ባለድርሻ አካላት ጋር ሰፊ ምክክርና ዝግጅት እያደረገ መሆኑን በተደጋጋሚ አስታውቋል።